Thursday, May 30, 2013

ጀብራሬው ‹‹ኢህአዴግ›› በአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ላይ



(አንድ አድርገን ግንቦት 23 2005 ዓ.ም)፡- ‹‹ ከምሽቱ 1፤30 ላይ አንድ ሞቅ ያለው የተበሳጨ ጀብራሬ አቡነ ጴጥሮስ  ሃውልት ላይ ሽንቱን እየሸና  ‹አንተ ድንጋይ ጓደኞችህ  ተመችቷቸው  በማርቼዲስ ሲንሸራሸሩ ይህው አንተ ድንጋይ ሆነህ ቀረህ ድንጋይ አሸናብሃለሁ › ሲል በልጅነት ደም ፍላት  ዘልዬ  ከጀብራሬው ጋር ግብ ግብ ገጠምኩኝ ፡፡ ድንጋይ አይደለም፡  ‹ድንጋይ ነው› በሚል በቡጢም  ተቃመስን ፡፡ ከስብሰባው የተበተኑ ሰራተኞች ገላገሉንና እየተበሳጨሁ ቤቴ ገባሁ፡፡ ሌሊቱን አልተኛሁም፡፡  ጴጥሮስ ሕያው ነህ ለማለት ፤ ጴጥሮስ ድንጋይ አይደለም ለማለት ይመስለኛል ‹ጴጥሮስ ያችን ሰዓት› ስጭር አደርኩ ›› ጸጋዬ ገብረ መድህን

ሃሙስ ሚያዚያ 24 ቀን 2004 ዓ.ም  ጠዋት ሳተና የሆኑ ወጣቶችና ጎልማሶች የአቡነ ጴጥሮስን ሃውልት ልክ እንደ አስቸጋሪ ኮርማ በገመድ ጠልፈው አንዳች የሚያህል ክሬነር አስረው ከነበረበት ለመንቀል ደፋ ቀና ይላሉ፡፡
አላፊ  አግዳሚው ወጪ ወራጁ እንደ ዘበት እያየ ያልፋል፡፡ ከፊሉም ሞባይሉን አውጥቶ ፎቶ ሊያነሳ እና ሊቀርጽ ይሞክራል፡፡ ‹‹የሰውየው›› (ሁነኛ ሰው) ሃውልት (የእኛ የእውነተኝነት) ዋቢ ከውስጥ በአቡጀዲ ተጠቅልሎ ፤ ከውጭ በጣውላ ተጠፍንጎ ፤ በብረት ዘንግ ተደግፎ ሊነቀል ትዕዛዝ ይጠብቃል፡፡

Wednesday, May 29, 2013

በዋልድባ ተዓምራቱ ቀጥሏል


  •  በዋልድባ የሰራተኞች መኖሪያ የቅዱስ ሚካኤል እለት ንፋስ በቀላቀለ ንፋስ ተጠራርጎ ጠፍቷል
  • በአፋር እና ትግራይ ክልል አካባቢ የሚገኘው ታሪካዊ እና እድሜ ጠገብ የመዝባ ገዳም እሳት ተለኮሰበት፣ አንድ ቤተመቅደስ ተቃጥሏል ሌሎችም ጉዳት ደርሶባቸዋል


(Save Waldba) :- እለቱ ግንቦት 12 ቀን ፳፻፭ ዓ.ም. ነው በዋልድባ ገዳም ዙሪያ በተለይ በዛሬማ ወንዝ አካባቢ የወልቃይት ስኳር ፋብሪካን ለመገንባት የሰፈሩት ሠራተኞች፣ መሃንዲሶች፣ የሥራ ተቋራጮች ብሎም ለዚህ ሥራ (ፕሮጀክት) ለማገዝ በአካባቢው ካምፕ ሰርተው ከሰፈሩ ወደ አንድ አመት ይጠጋቸዋል። እነዚህን ሠራተኞች ለማስቀመጥ በርካታ ቤቶች፣ የሚመገቡበት የምግብ አዳራሽ፣ ለሥራ ተቋራጮች እና ለማሀንዲሶች ቢሮዎችን በተጨማሪ ለሥራው የሚጠቀሙበትን መሳሪዎች የሚቀመጡበት መጋዘኖችን ጨምሮ ቦታው በርካታ ቤቶችን እና ትላልቅ መጋዘኖችን የያዘ በዛሬማ ወንዝ ሰሜን በኩል ኮረብታ ላይ የተከተመ ቦታ ነበር። “በፊቱ ተጠንቀቁ፥ ቃሉንም አድምጡ ስሜም በእርሱ ስለ ሆነ ኃጢአት ብትሰሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት” ዘጸዓት ፳፫ ፥ ፳፩  አረማውያን በየዜው የጌታን ትዕዛዝ በመተላለፍ በቤቱ በድፍረት እና በትዕቢት የሚያደርሱትን በደል እየተመለከተ በቁጣው የተግሳጽ ድምፁን ሲያሰማ ቢቆይም እነርሱ ግን ሊሰሙ አልቻሉም እግዚአብሔርም ትዕዛዛሩን በመልዕክተኞቹ በባለሙዋሎቹ እያስተላለፈ ነው ፣ ልቡ ለተሰበረ በፈጣሪ አምላካችን እምነት እና ድህነትን ማግኘት የፈለገ የምሕረት አባት ነውና ሁሌም ጎበኘናል ነገር ግን የፈርዖን ልጆችን በባሕረ ቀይ ባሕር የበላ ዛሬም በየጉድባው ለሚጸልዩት አባቶቻችን መልሱን እየሰጠ ነው በለፉት አንድ አመት ብቻ መድኅኒዓለም ክርስቶስ በርካታ ታዓምራቱን በገዳሙ አካባቢ ስኳር እመርታለን ያሉትን እድሜ ለንሰሃ እየሰጠ ሥራቸውን ግን እንደ ባቢሎን ግንብ እያመከነው ይገኛል ፥ ልክ ባቢሎናውያን አምላክን እናገኘዋለን ብለው ግንብ ሲገነቡ በመጨረሻ ድፍረታቸው ስለበዛ ቋንቋቸውን ቢቀላቅልባቸው እላይ ያለው ሲሚንቶ ሲጠይቅ አፈር ይዞለት ይመጣ ነበር በመሆኑም ሥራቸው መክኖ አምላክም ክብሩ የተገለጸበት ጊዜ እንደነበር መጽሐፍ ቅዱሳችን ቁልጭ አድርጎ ይናገል፥ ዛሬም ፈጣሪ እለት ተእለት የሚሰለስበትን፣ የሚቀደስበትን ቅዱስ ቦታ ለማፍረስ እና ታሪክን እና የወገን ሃብትን ለማጥፋት የተዳደሩትን ልክ እንደ ባቢሎናውያኑ ቋንቋቸው ባይጠፋም እርስ በእርስ መግባባት እስኪሳናቸው ድረስ ማድረግ የሚችል የሠራዊት ጌታ ዛሬም እነዚህን አረማውያን አንዴ በቁጣው ሲገስጻቸው፣ ሌላ ጊዜ ሥራውን ሊሰራ የመጣውን ካምፓኒ ሲያበረው ተግዳሮታቸውንም በድፍረት እና በማናለብኝነት እንደቀጠሉ ነው እውን እዳር ያደርሱት ይሆን?

Monday, May 27, 2013

ግንቦት 20 ሊደረግ የታሰበው ጉባኤ ተሰረዘ




(አንድ አድርገን ግንቦት 19 2005 ዓ.ም)፡- ግንቦት 20 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት አንስቶ በአጥማቂ መምህር ግርማን በተመለከተ በተለምዶ አራት ኪሎ ግቢ ገብርኤል ተብሎ በሚጠራው ቤተክርስቲያን(መንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል) ሊካሄድ የታሰበው ጉባኤ በአንዳንድ ምክንያቶች ተሰረዘ፡፡   ወደፊት ብዙ ምዕመናንን መያዝ አቅም ባለው አዳራሽ ጉባኤው ይዘጋጃል ተብሏል፡፡

Friday, May 24, 2013

የ‹‹አጥማቂው› መምህር ግርማ ስራ በቤተክርስቲያን ስርዓት እይታ



(አንድ አድርገን ግንቦት 16 2005 ዓ.ም)፡- መምህር ግርማ የማጥመቅ ስራቸውን ከጀመሩ ዓመታት ማስቆጠራቸው  ይታወቃል ፤ በየሄዱበት ብዙ ተከታይ ከማፍራታቸው በተጨማሪም ብዙ ነቃፊ ፤ ትምህርታቸውም ይሁን የማጥመቅ ስርአታቸው ከቤተክርስቲያን ውጪ ነው የሚሉ ሰዎች አልታጡም ፤ ‹‹አጥማቂው›› በተለይ በቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ሲያካሂዱት የነበረው ተግባር 17 ክፍል ያለው ፊልም ወደ ሲዲ በመለወጥ ለህዝበ ክርስቲያኑ ለገበያ አቅርበዋል፡፡ ምዕመኑ ቤተክርስቲያን ሄዶ ከማስቀደስ ይልቅ የእሳቸውን ሲዲ ከፍቶ ቤቱ ቁጭ ብሎ ‹‹ይገርማል›› እያለ የሚያይበት ጊዜም ነበር ፤ ከሀገር ውጪ ያሉ አብያተክርስቲያናት ‹‹አጥማቂውን›› አምጡልን በማለት የቤተክርስቲያኖቻቸው አስተዳዳሪዎች ያስጨነቁበት ጊዜም ነበር ፤ በአሁኑ ሰዓት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ በብዙ ምዕመናን ቤት የ‹አጥማቂው›› ፊልሞች ይገኛሉ፡፡ ከቀናት በፊት የቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን ካገዳቸው በኋላ ቤተክህነቱ እንዲህ በማለት ድጋፉን ገልጾላቸዋል ‹‹መምህር ግርማ ወንድሙ በደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ በሕገ ወጥ መንገድ የሚፈጽሙት ሕገ ወጥ የማጥመቅ ሥርዐትና የወንጌል አገልግሎት መኾኑን እየገለጽን የእምነታችን ተከታይ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከዚህ እግድ ጋራ በተያያዘ የጸጥታ ችግር እንዳይገጥመው የሰበካ ጉባኤ /ቤት ጥብቅ ክትትል በማድረግ ውሳኔውን ተግባራዊ እንዲያደርግ እያሳሰብን የሚመለከታቸው የመንግሥት የጸጥታ አካላትም የቤተ ክርስቲያኒቱን ውሳኔ ተግባራዊ በማድረግ ረገድ አስፈላጊው ትብብር እንዲያደርጉልን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡››
 
ይህ በእንዲህ እያለ የ‹አጥማቂው›› የሲዲ ስራዎች በቤተክርስቲያ እይታ ምን ይመስላሉ ? እውን ትምህርታቸውም ሆነ የአጥምቆት ስርዓታቸው የቤተክርስቲያን ስርዓትን የተከተለ ነውን? ምዕመኑ ለምን አላስፈላጊ ንትርክ ውስጥ በ‹‹አጥማቂው›› አማካኝነት ሊገባ ቻለ? ‹‹መምህር›› ግርማስ ማን ናቸው ? እና በ‹‹አጥማቂው›› ዙሪያ የሚነሱ ጉዳዮችን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ባሉበት ግንቦት 20 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡00 ጀምሮ በአራት ኪሎ ግቢ ገብርኤል አዳራሽ በምዕመናን ታላቅ መልስ የመስጠት ጉባኤ ተዘጋጅቷል፡፡ በ‹‹አጥማቂው›› ግራ ለገባችሁ ፤ ግራ ለተጋባችሁ ፤ ግራም ያጋባችሁ ሁላችሁም በጉባኤው ላይ ተጋብዛችኋል፡፡

ጥንተ አብሶ እና ተዋሕዶ




በሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

(አንድ አድርገን ግንቦት 16 2005 ዓ.ም)፡- በነገረ ሃይማኖት ውስጥ እስከ አሁን ድረስ ሆኖ እንዳየነው፣ እንደሚያታወቀው፣ እየሆነም እንደምናየው ከባለቤቱ ከመድኀኔዓለም ክርስቶስ አንሥቶ መትሕተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን በሆነችው በቅድስት ድንግል ጽዮን ማርያም፣ በቅዱሳን መላእክት፣ በአበው ጻድቃን ሰማዕታት /ቅዱሳን/ በሁሉም ላይ ክሕደት ወይም ኑፋቄ ያልተነሣበት ማንም የለም፡፡ በወላዲተ አምላክ ላይም ከሚነሡ ኑፋቄዎች ሁሉ የከፋውና ከባዱ ኑፋቄ ደግሞ ይህ ከላይ በርእስ የተጠቀሰው የኑፋቄ ወይም የክሕደት ዓይነት ነው፡፡ ክሕደት ወደነው አይመጣም በቦታና በጊዜም አይወሰንም፡፡ አሳች ሰይጣን እስካለ ጊዜ ድረስም ይቀጥላል፡፡ የሥጋ ሞት ለሰው ልጆች ሁል ጊዜ እንግዳ እንደሆነ ሁሉ የነፍስ ሞት ኑፋቄ ወይም ክሕደት ደግሞ ሁል ጊዜ እንግዳ ነው፡፡ 


ምንም እንኳን ክሕደት ወይም ኑፋቄ በየዓይነቱ እንደሚነሡ እንደሚመጡ ከክርስቶስ ጀምሮ ደቀ መዛሙርትም በወንጌልና በየመልእክቶቻቸው አስቀድመው ያስጠነቀቁና ያሳሰቡ ቢሆንም ጉዳዩ በቅዱሳት መጻሕፍት በግልጽ ይቀመጥም አይቀመጥ ኑፋቄ ወይም ክሕደት ያልተነሣበት የጉዳይ ዓይነትም የለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ወይም መጽሐፍ ቅዱስ በቁሙ የምሥጢር መጽሐፍ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሲናገርም በቀጥታ ግልጽ ባለ ቋንቋ ከመናገር ይልቅ በምሳሌ ማስረዳትን ይመርጣል፡፡ ወንጌልን ስናነብ ማለትም የጌታን ትምህርት ያየን እንደሆነ ያለ ምሳሌና ምሥጢር የተናገረው ቃል የለም ማለት ይቻላል፡፡ አስቀድሞ ‹‹አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ›› ተብሎ ተጽፏልና፡፡ 

Monday, May 13, 2013

የዲሞክራሲን ሥርዓት ምንነት ያለመረዳት ችግር የፈጠረው መወናበድ በፌዴራል ጉዳዮች ሚንስቴር የእምነት ተቋማትን ለመቆጣጠር በወጣ መመሪያ ሲገለጽ፡-



ሠዓሊ አምሳሉ /ኪዳን አርጋው
amsalugkidan@gmail.com

ከጽሁፉ የተወሰደ

  • የዚህ መመሪያ ግብም እንደመመሪያው አርቃቂዎች እምነት የእምነት ተቋማቱን እግዚአብሔር (ፈጣሪ) ከሚባለው ምናባዊ ነገር እንዲራራቁና እንዲረሳሱ በማድረግ የእነሱ ጉዳይ ፈጻሚዎችና አምላኪዎች እንዲሆኑ በማድረግ ሊፈጥሯት የሚፈልጓትን ከማንነቷ ፣ከታሪኳ ፣ከመለያዎቿ ተለያየችና የተካካደች አዲስ ሀገርና ሕዝብ መፍጠር ነው፡፡
  •  ስናያቸው ኢትዮጵያዊያን ይመስላሉ ወይም ናቸው ምን ነው ታዲያ በገዛ ማንነታቸው ላይ የጥፋት ዘመቻ ላይ መጠመዳቸው? ምን የሚሉት በሽታ ነው ይሄ? ይሄን ሁሉ ጉድ እውን የራስ ዜጋ ያደርገዋል ብሎ ማሰብ እንዴት ይቻላል?
  • የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የኢትዮጵያዊነት መገለጫ እና መለያ ናትና፡፡ የኢትዮጵያዊነት መገለጫዎችን፣እሴቶችን ጠልቶ ኢትዮጵያዊ ነኝ ማለት አይቻልም ፤ይህች ቤተክርስቲያን ለሀገራችን ብቻ ሳይሆን ከራሷ አልፋ ለመላው ዓለም የዋለችው ቁም ነገር ሁሉ እጅግ ብዙና ውለታን ለሚያስብ ኅሊናም ላለው የሰው ፍጡር ሁሉ ውለታዋ ከክብደቱ የተነሣ የሚያስጨንቅና ዕረፍት የሚነሳ ነው
  • ኢትዮጵያ ሃይማኖት ከየትም አልመጣላትም፡፡ የመጣለት ነገር ቢኖር ኪዳናቱ ብቻ ናቸው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኢትዮጵያ ከመቼ ጀምሮ በእግዚአብሔር እንዳመነች አልተገለጸም፡፡ የሚታወቀው ነገር ቢኖር ከቀደሙት የቀደምን መሆናችን ብቻ ነው፡፡


(አንድ አድርን ግንቦት 5 2005 ዓ.ም)፡- መሰንበቻውን የፌዴራል ጉዳዮች ሚንስቴር የእምነት ተቋማትን ለመመዝገብ (ለመቆጣጠር) አንድ መመሪያ ማውጣቱና እያነጋገረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህ መመሪያ የተረቀቀውና ተግባራዊ ሊደረግ ታስቦ የነበረው በተመሳሳይ ዓላማና አንቀጾች በተለያዩ ሰብአዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተሰማርተው ይሠሩ የነበሩትን መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን (NGOs) ያሽመደመደው ፣ መፈናፈኛ ያሳጣውና ከአገልግሎት ውጪ ያደረገው ደንብ ወይም መመሪያ ወጥቶና ተግባራዊ ሆኖ ለዓላማቸው አመርቂ ውጤት እንዳስመዘገበላቸው ባወቁ ጊዜ ነበር፡፡ ይህንን ውጤት በማየትም በተመሳሳይ መልኩ ደንቡን ወይም መመሪያውን በሃይማኖት ተቋማትም እንዲፈጸም ቢያደርጉ የልባቸው ሊደርስ እንደሚችል እምነት አሳድረው በመንቀሳቀስ ላይ እንዳሉ በመሀሉ ያልታሰቡ ሁለት የሞት አደጋዎች በመከሰታቸው እስከአሁን ሊቆይ ቻለ፡፡ አሁን ቀጥታ ወደ መመሪያው ዝርዝር ጉዳዮች ገብቼ ይሄ ይሄ ከማለቴ በፊት ለዚህና መሰል የቤተክርስቲያንን ጥቅም ለሚጋፉ መመሪያዎች መውጣትና መተግበር መሠረት ወደ ሆነው የተሳሳተ አስተሳሰብ ተመልሼ ጥቂት ብል ነገሩን በሚገባ ግልጽ ያደርገዋልና መለስ አድርጌ ልያዛቹህ፡፡